Search This Blog

Tuesday, January 10, 2017

በእነጉርሜሳ አያኖ መዝገብ 5ት ቀሪ የአቃቤ የህግ ምስክሮችን ለመስማት ተጨማሪ ቀን ተሰጠ [የታህሳስ 27/4/2009 ውሎ]

FREE ALL POLITICAL PRISONERS !!!
አቃቤህግ ቀሪ ምስክሮች ቀርበው እንደሆነ ሲጠየቅ፤ አምስት ምስክሮች እንደሚቀሩት እና ተገቢውን ጥረት ቢያደርግም ሊቀርቡ እንዳልቻሉ በመግለፅ የበለጠ ጉዳዩን እንዲያስረዱለት ከፓሊስ የቀረቡትን ረዳት ኢንስፔክተር ቴድሮስ አዳነ ጠይቋል። ረዳት ኢንስፔክተሩ የተሰጣቸው ጊዜ አጭር በመሆኑ በተሰጠው ቀጠሮ ሁሉንም ማቅረብ አለመቻላቸውን፤ ምስክሮቹ አካባቢያቸውን አበመልቀቃቸው በአዲሱ አድራሻቸው እያፈላለጓቸው በመሆኑ፤ ራቅ ያለ ቦታ ያሉ ምስክር በመኖራቸው ከፍተኛ የጊዜ እጥረት ስለገጠማቸው በመሆኑ ጊዜ እንዲጨመርለት ጠይቋል። በመቀጠልም አቃቤ ህግ ከቀሩት 5 ምስክሮች ውስጥ አንዱ ጉጂ ዞን የሚገኝ፣ አንዱ ፀበል ላይ እንደነበረ እና ማስረጃ እስኪያመጣ ጊዜ ስላጠረ፣ አንደኛው አድራሻ ቀይሮ ሌላ ቦታ በመሄዱ በተሰጠው ጊዜ ቀርበው መመስከር እንዳልቻሉ ተናግሮ የተቀሩት ሁለቱ ግን የአዲስ አበባ ነዋሪ መሆናቸውን መመስከር ስላልፈለጉ አድራሻቸውን እየቀያየሩ እንዳስቸገሯቸው ተናግሯል። እስካሁን ይመሰክራሉ ከተባሉ 42 ምስክሮች ውስጥ 37ቱን እንዳሰማ የተናገረው አቃቤ ህግ የተከሰሱበትን የክስ ክብደት እንዲሁም ከፍተኛ ጉዳት ያስከተለ ተግባር መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ቀሪ ምስክሮችን አቅርበው እንዲያሰሙ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።
የተከሳሽ ጠበቆች የተሰሙት ምስክሮች በችሎቱ ግፊት እንጂ አቃቤ ህግ ዳተኛ እንደነበረ፤ ምስክሮቹን ማቅረብ ስላልፈለገ እንጂ በቂ ጊዜ ተሰጥቶት እንደነበረ፤ የፍትህ ሂደት የሚለካው በሂደቱም ጭምር መሆኑን፤ ከባለፈው ቀጠሮ ጀምሮ በሰበብ አስባቡ ምስክሮችን ለማምጣት በሚል ቀጠሮ መሰጠቱን ተቃውመው እንደነበረ እና የዛሬው ቀጠሮም የመጨረሻው በሚል የተያዘ እንደሆነ ገልፀው ተጨማሪ ቀጠሮ መሰጠት እንደሌለበት ተናግረዋል።
"እንደሚታወቀው ከታሰርን ሁለት ወራችን አይደለም። አንድ አመት አልፎናል። እነሱ ቤታቸው እያደሩ እኛን እያሾፉብን ነው። በአንድ ቀን ብዙ ሺዎችን እያሰረ ያለ መንግስት፤ እንዴት ነው 5 ምስክሮችን ማቅረብ ያልቻሉት? " በማለት የኦፌኮ /ፕሬዝዳንት አቶ በቀለ ተጨማሪ ቀጠሮ መኖር የለበትም ሲሉ ተከራክረዋል። አቶ ደጀኔ ጣፋም ተቃውሟቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል። "አቃቤ ህግ ሲናገር 2 አዲስ አበባ ናቸው ብሏል። ለምን አልቀረቡም እስካሁን? ክሳችን መጀመሪያም የፓለቲካ ክስ ነው አሁንም የፓለቲካ ድምዳሜ ነው የምንሰማው። እንዲሁ እንደከሰሳችሁን እንዲሁ ፍረዱብን። ወይስ ፍትህ አለ ለማስባል ነው? የኛን እና የናንተን ጊዜ ለምን ይፈጃሉ? ጉጂ እኮ ወርቅ የሚዘረፍበት ነው። እንዴት ከዛ አንድ ሰው ማምጣት ይከብዳቸዋል? አቃቤ ህግ ሌላ ጫና ከሌለባቸው በህጉ አግባብ ይስሩ። ፍርድ ቤት በየጊዜው እያሳሰሰባቸው ነው ምስክር ይዘው ሚቀርቡት። ያልቀረቡ ምስክሮችን በተመለከተ ከቀበሌ ደብዳቤ ይዘው ቀርበዋል ወይ? አልቀረቡም! የፍርድ ቤት ትእዛዝ እየተከበረ አይደለም። እናንተም የካድሬ አይነት ሳይሆን የባለሙያነት አሰራር ስሩልን።" በማለት ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱን እንደሚቃወሙ ተናግረዋል።
"አቃቤ ህግ ዛሬ አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን ብሏል በወቅቱ ቀጠሮ ሲሰጥ ለምን አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን አይበቃንም አላለም? ከቀበሌ ይቅረብ የተባለው ማስረጃ አልቀረበም። የችሎቱ ብይን መከበር አለበት። ማእከላዊ ሲያሰቃዩን የነበሩ ፓሊሶች ናቸው ዛሬ ቀርበው ያልተገባ ተጨማሪ ቀጠሮ እየጠየቁ ያሉት።" ሲል የተጨማሪ ቀጠሮውን ጉዳይ ተቃውሞ አሰተያየታቸውን የሰጡት አቶ አዲሱ ቡላላ ናቸው።
ዳኞች ከተማከሩ በኋላ አቃቤ ህግ ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ፤ ተከሳሾችን ደግሞ የፓለቲካ እስረኛ ብሎ ነገር እንደሌለ፣ ያሉበትን ሁኔታ እንደሚረዷቸው፣ እንዲያውም ማነፃፀር ባይገባም ከሌላው መዝገብ ሲተያይ በፍጥነት እየሄደ መሆኑን፣ እነሱም [ተከሳሾች] መከላከያ ምስክር በሚያሰሙበት ጊዜ ምስክሮችን ለመስማት ጊዜ እንደሚሰጡ በመግለፅ ፓሊስ 15 ቀን ውስጥ ከየትም ፈልጎ ምስክሮቹን እንዲያመጣ፤ የማይገኙ ከሆነም ይኖሩበት ከነበረው ቀበሌ ደብዳቤ እንዲቀርብ ትእዛዝ ሰጥተዋል። አቃቤህግ የተሰጠው ጊዜ አጭር እንደሆነ በመግለፅ ትንሽ ረዘም ያለ ቀጠሮ እንዲሰጠው ቢጠይቅም ዳኞች ጥያቄውን ሳይቀበሉት፤ ፓሊስ የተቻለውን ሁሉ ጥረት በማድረግ በቀጠሮው ቀን እንዲያቀርብ አዘዋል።


የተከሳሽ ጠበቃ የሆኑት አቶ መልካሙ የሚሰጠው ቀጠሮ የመጨረሻ እንዲሆን በሚል ላቀረቡት ሃሳብ፤ የመጨረሻ ቀጠሮ የሚባል እንደሌላ አሳማኝ ምክንያት ከተገኘ ሌላ ቀጠሮ ሊሰጥ እንደሚችል፤ አሳማኝ ምክንያት ካልተገኘ የመጨረሻ ባይባልም የምስክር የመስማት ሂደት ሊቋረጥ እንደሚችል በመጥቀስ ቀጣዩ ቀጠሮ የመጨረሻ መባል የለበትም ሲሉ ዳኞች መልስ ሰጥተዋል።

ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 15/2009 ቀጠሮ ተይዟል።

No comments:

Post a Comment