Search This Blog

Sunday, January 10, 2021

ለፖለቲካ ችግሮቻችንም ሆነ ለነፃ፣ ፍትሓዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ የፖለቲካ ምህዳሩ መስፋቱ ወሳኝ ነው!

ለፖለቲካ ችግሮቻችንም ሆነ ለነፃ፣ ፍትሓዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ የፖለቲካ ምህዳሩ መስፋቱ ወሳኝ ነው!
-----
በወቅታዊ የአገራችን ጉዳይ ላይ ከኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ-ኦፌኮ (
Oromo Federalist Congress - OFC
- ) የተሰጠ መግለጫ
-----

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ ከምስረታው ጀምሮ በሠላማዊ ውይይትና ድርድር የሚያምንና የአገራችንን ፖለቲካዊ ችግሮችን ለመፍታት መነጋገር፣ መወያየትና መደራደር አስፈላጊ እንደሆነ ሲያሳስብ የቆየ ድርጅት ነው፡፡ በነፃ፣ ፍትሓዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ የመንግስት ሥልጣን መያዝን ዓላማ አድርጎ ሲንቀሳቀስ እንደቆየ ይታወቃል፡፡ በዚሁ መሠረት የፌዴራል ሥርአቱ ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲተገበር፣ በክልሎች የራስ አስተዳደር ውስጥ ጣልቃ ገብነትና የሞግዚት አስተዳደር እንዲወገድ በኢህአዴግ በሚመራው መንግስት ላይ ለዓመታት የመረረ ትግል በማድረጋችንም አያሌ አባሎቻችን ከባድ መስዋዕትነትን ከፍለዋል፡፡ ከማዕከል እስከ ታችኛው እርከን የነበሩ የኦፌኮ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ላይ የግድያ፣ የማሰር፣ የማሰቃየት፣ የማፈናቀልና የማሳደድ ወንጀል ተፈፅሞባቸዋል፡፡ ዛሬም ስፍር ቁጥር የሌላቸው የኦፌኮ አባላትና ደጋፊዎች ከከፍተኛ አመራር እስከ ታችኛው እርከን ድረስ ያሉት ለሕዝባቸው መብትና ነፃነት ፀንተው በመቆማቸው ምክንያት ብቻ የውሸትና የፈጠራ ወንጀል ተለጥፎባቸው በአገሪቱ የተለያዩ ማጎሪያ ካምፖች ማለትም በፖሊስ ጣቢያዎች፣ በልዩ ኃይል ካምፖች፣ በድርጅት ጽ/ቤቶች፣ በመደበኛ እስር ቤቶችና በመማርያ ክፍሎች ጭምር ታስረው እየተሰቃዩ ይገኛሉ፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ የወቅቱን የኢትዮጵያ ችግሮችን በመጠቀም የቀኝ ኃይሎች በቅርፅ ያገኘነው ሕብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝሙ በዛ ብለው ሕገ መንግስቱንና ማንነትነ መሠረት አድርገው የተመሰረቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከፖለቲካ አውዱ እንዲወጡ ግፊት ማድረግ ጀምረዋል፡፡ የብሔሮች ጥያቄ ሕወሓት ከመመስረቱ በፊት ሲጠየቅ እንደነበረ ተረስቶ ከሕወሓት ጋር መኮነኑን ሥራቸው ያደረጉ ድርጅቶች እየበዙ ነው፡፡ እነዚህ የቀኝ ኃይሎች በጊዜ ሃይ ሊባሉ ይገባል እንላለን፡፡
እንደ የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ ዓላማ የኦሮሚያ ክልል ሕዝቦች በተመሰረተው ሕብረ ብሔራዊ የፌዴራል ሥርአት ውስጥ በሕዝቦች ፍላጎትና በዴሞክራሲያዊ ምርጫ ብቻ ውክልና እንዲኖረውና በማንነቱ ሳይሸማቀቅ ከማንም ሳያንስና ሳይበልጥ ራስን በራስ የማስተዳደር ዴሞክራሲያዊ መሠረታዊ መብቱ ዓለም አቀፋዊ መርሆዎችን መሠረት አድርጎ እንዲከበርለት ማስቻል ነው፡፡ ሆኖም ሕገ መንግስቱንና በሕገ መንግስቱ መሠረት የተዋቀረውን ሕብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝሙን የሚቃወሙ የቀኝ ኃይሎች በአንድ በኩል ግፋ በለው! ሲሉ፤ የመንግስት በትረ ሥልጣኑን የተቆጣተሩት ደግሞ የፌዴራል አወቃቀሩ እንዲቀለበስ ሲንቀሳቀሱ ይታያሉ፡፡ ይህ አደገኛ አካሄድ እንደሆነ ኦፌኮ ይገነዘባል፡፡

ዛሬ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች እየተፈጠሩ ያሉ ብሔር ተኮር ግጭቶች ሁሉንም ወገን አሳታፊ በአደረገ መንገድ እንዲፈቱ ከቆምንለት የሰላማዊ ትግል መርህ አንፃር የጦርነት አማራጭ ድሃዋን አገራችንና የሕዝባችንን ጥቅም እንደሚጎዳ፣ ብሎም ያገራችንን ውድቀት ሊያፋጥን ይችላል ከሚል ሥጋት የተነሳ ኦፌኮ ፖለቲካዊ ችግሮች በብሔራዊ መግባባት እንዲፈቱ ሲያሳስብ ቆይቷል፡፡ መንግስትም ሆነ ገዥው ፓርቲ እየሰሙን አይደለም፡፡ ይበልጥ የሚገርመው ደግሞ መንግስት፣ ገዥው ፓርቲ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ለሦስት ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ ብሔራዊ መግባባት ብለን ከአዲስ አበባ እስከ አርባ ምንጭ እና ቢሾፍቱ ድረስ የተለፋበትን ሥራ ወደ ጎን በመተው ስድስተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ለማካሄድ የጊዜ ሰሌዳ አወጥተዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ተካሄዱ የሚባሉ አምስቱም ዙር ምርጫዎች ነፃ፣ ፍትሓዊና ተአማኒ ያልነበሩና ዓለም አቀፍ መመዘኛዎች ያላሟሉ ናቸው በማለት ተወዳዳሪ ፓርቲዎች፣ የኢትዮጵያ ሕዝቦችና ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች ዕውቅና እንዳልሰጡት ይታወቃል፡፡ አሁንም ባለው ሁኔታ የመንግስትና አጋሮቹ አያያዝ መጪው ምርጫም ቢሆን ነፃ፣ ፍትሓዊና ተአማኒ ይሆናል ብሎ መጠበቅ የዋህነት ይመስላል፡፡
ስለሆነም፤ የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) ለአገራችን ውስብስብ ችግሮች እና ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርአት ለመሸጋገር አሳታፊ የሆነ ድርድርና ውይይት እንዲደረግ ጠይቆ ሰሚ ጆሮ ቢያጣም፤ ዛሬም የሚከተሉትን ጥያቄዎችና የመፍትኼ ሐሳቦችን እናቀርባለን፡፡

1. የኢፌዲሪ መንግስት በሕገ መንግስቱና አገራችን በተቀበለቻቸው ዓለም አቀፍ ሕጎች የተደነገጉትን ሰብአዊና ዴሞክራሲያ መብቶችን በማክበር በተለያዩ የአገሪቱ አከባቢዎች በፖለቲካ አቋማቸው ምክንያት ያሰራቸውን የፓርቲያችንን አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎችን በአስቸኳይ እንዲፈታና የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት እንድንቀሳቀሱ ዋስትና እንዲሰጥ፤ እንዲሁም በመንግስት ኃይሎች የተዘጉ ጽ/ቤቶቻችን ተከፍተው ሥራ እንዲጀምሩ ሁኔታዎች እንዲመቻቹልን አበክረን እንጠይቃለን፡፡ ምርጫውን የሚያስተባብሩ፣ የሚወዳደሩ እና የሚታዘቡ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ታስረው፣ ሌሎችም ከደረሰባቸው ማስፈራሪያ የተነሳ ተሰድደውና ጽ/ቤቶቻችን በኃይል ተዘግተው ምርጫውን ለመሳተፍ እጅግ አስቸጋሪ እንደሚሆንብን ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝቦችና ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ለማሳወቅ እንወዳለን፡፡

2. በሀገሪቱ የተለያዩ አከባቢዎች የተሰማሩ የፖሊስ፣ የልዩ ኃይልና ሚሊሻ አመራሮችና አባላት ከፓርቲ ፖለቲካ ወገንተኝነት ነፃ ሆነው የዜጎችን ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶች በማክበር እንዲሰሩ መንግስትና ገዥው ፓርቲ በአስቸኳይ ሁኔታውን እንዲያመቻቹ እናሳስባለን፡፡

3. በመንግስት የሚተዳደሩ የመገናኛ ብዙሃን የገዥውን ፓርቲ ፍላጎት ብቻ እያንፀባረቁ ይገኛሉ፡፡ ከመንግስት ጋር ጥብቅ ግንኙነት ያላቸው አንዳንድ የግል ነን የሚሉ ሜዲያዎች ደግሞ መንግስት ብሔር፣ ብሔረሰብን መሠረት አድርገው የተቋቋሙ ፓርቲዎችን ለማጥፋት የኃይል እርምጃዎችን እንዲወስድ ውረድ በለው! ግፋ በለው! የሚለውን ነጠላ ዜማ ያቀነቅናሉ፡፡ እንዴዚህ ዓይነት አካሄድ ሀገራችንን አይጠቅማትም፡፡ ስለሆነም፤ ሜዲያዎች ሁሉ ለኢትዮጵያዊያን መረጃ በማቅረብ ሕብረተሰቡ ስለአገራችን አጠቃላይ ሁኔታ እንዲረዳ በትጋት እንዲሰሩና ሙያው ግዴታቸውን እንዲወጡ በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን፡፡

4. ሕግ የሚወጣው የዜጎችንና የአገርን ደህንነት ለማስጠበቅና ዋስትና ለመስጠት ሲሆን ሕግና ሥርአት በማይከበርበት አገር ውስጥ ሠላም፣ ልማትና ብልፅግና ተደጋግሞ ስለተናገሩት ብቻ አይታሰብም፡፡ በሕገ መንግስቱ ከተደነገገው ውጭ በተለያዩ አከባቢያዎች ሕገ ወጥ ግድያዎች፣ ሕገ ወጥ እስር፣ ማፈናቀል፣ ማስፈራሪያዎች በዜጎች ላይ እየደረሱ ይገኛሉ፡፡ ፍርድ ቤቶች እንድፈታ ያዘዙትን ዜጋ በማን ትዕዛዝ እንደሆነ በማይታወቅበት ሁኔታ ፖሊስ መልሶ ያስራል፡፡ በመንግስት ኃላፊነት ሽፋን ወንጀል የፈጸሙ የመንግሰት ባለሥልጣናት ለሕግ አይቀርቡም፡፡ ቢቀርቡም በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ ስለሆነም ፍርድ ቤቶች፣ ወንጀል መርማሪ የፖሊስ አካላት ከማንኛውም ፓርቲም ሆነ ቡድን ወገንተኝነት ራሳቸውን ነፃ በማድረግ ለመልካም አስተዳደር እና ዴሞክራሲ ግንባታ የሚደረገውን ጥረት እንድታግዙ ጥሪ እናደርጋለን፡፡

5. የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በሀገሪቱ የተለያዩ አከባቢዎች በመዘዋወር እየተፈጸሙ ያሉትን ኢሰብአዊና ኢዴሞክራሲያዊ ድርጊቶችን በመከታተል በሕግ የተሰጣችሁን ግዴታ እንዲትወጡና ወገኖቻችንን ከዕልቂት ለመታደግ ሚናችሁን እንድትወጡ አደራ እንላለን፡፡

6. በአሁኑ ወቅት የአገራችን የፖለቲካ ኃይሎች ልዩነቶቻችንን አጥብበን ሀገራዊ መግባባትን በመፍጠር የተሳካ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር የምናደርግበት ወሳኝ ጊዜ ላይ እንገኛለን፡፡ መንግስት፣ ገዥው ፓርቲና የኢትዮፕያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ነፃ፣ ፍትሓዊና ሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት የሚኖረው ምርጫ ይካሄድ ዘንድ የገፋበትን ገታራ ፖሊሲያቸውን አቁመው ምቹ የፖለቲካ ምህዳር እንዲፈጠር እንዲያደርጉ አበክረን እንጠይቃለን፡፡

በማጠቀላያችን፤ ለኢትዮጵያ ሕዝቦችና ለታሪክ በግልፅ መተው የምንፈልገው ፖለቲካችንን ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ማሰልጠን አቅቶን ከአንዱ ቀውስ ወደ ሌላ ቀውስ፣ ከአንዱ ሽግግር ወደ ሌላ ሽግግር ስንዳክር ኖረናል፡፡ ውጡቱም እየታየ ነው፡፡ ከቅርብ ታሪካችንም ለመማር ባለመታደላችን ላለፉት ሦስት ዓመታት ብሔራዊ መግባባት ላይ ለመድረስ ቄሶችና ሼኮችን፣ አባ ገዳዎችና የአገር ሽማግሌዎችን ያስቸገረ ሁኔታ ውስጥ ገብተናል፡፡ ትርፍና ኪሳራውንም ከኢትዮጵያ ሕዝቦች ጋር እያየን ነው፡፡ ላለፉት ሦስት ዓመታትም ለተሳካ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር የጋራ ፍኖተ ካርታ ቀርፄን ተስፋ የተጣለበትን ዴሞክራሲያዊ ሥርአት ለማምጣት በብሔራዊ መግባባት የታጀበና ውል ያለው ስምምነት ላይ ሳንደርስ ሰላማዊ፣ ነፃና ፍትሓዊ ምርጫ ይቻላል ብለን በሕልሞቻችን እየዳከርን ነው፡፡ ስለሆነም፤ የሞኝ ሩጫ እንዳይሆንብን በሐቅ ለሕዝቦቻችሁ መብትና ነፃነት የተደራጃችሁ ሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎችና የኢትዮጵያ ሕዝቦች ሀገራችንን ከገባበችበት አስቸጋሪ ጊዜ በጋራ እንድናወጣት ድርጀታችን በአክብሮት ጥሪውን ያቀርባል፡፡
ለተሳካ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ብሔራዊ መግባባት አማራጭ የለውም!
---
የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ)
/013 ዓም

No comments:

Post a Comment