Search This Blog

Wednesday, November 12, 2014

አቃቢ ህግ በጦማርያኑና ጋዜጠኞቹ ላይ የመሰረተውን ክስ እንዲያሻሽል ታዘዘ

ክሱ ተሻሽሎ መቅረቡን ለማየት ለህዳር 24 ቀጠሮ ተሰጥቷል
የፌደራል አቃቢ ህግ በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በጦማርያኑና በጋዜጠኞቹ ላይ የመሰረተውን የሽብር ክስ እንዲያሻሽል የልደታ ከፍተኛ ችሎት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
FREE ZONE 9 BLOGGERS!!!

ፍርድ ቤቱ ዛሬ ህዳር 3/2007 ዓ.ም በዋለው ችሎት ቀደም ብሎ የተከሳሽ ጠበቆች ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያ መርምሮ ብይን በመስጠት በንባብ አሰምቷል፡፡ በዚህ መሰረትም ፍርድ ቤቱ በክስ መቃወሚያው ላይ የቀረቡትን ዝርዝር ነጥቦች መርምሮ በተወሰኑ ነጥቦች ላይ አቃቢ ህግ ክሱን እንዲያሻሽል ትዕዛዝ ሲሰጥ፣ በሁለተኛነት ቀርቦ የነበረው የክስ ይዘት በአንደኛው የክስ ይዘት ላይ መጠቃለል ስለሚችል ሁለተኛውን የክስ ይዘት ፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡
በክስ ዝርዝሩ ላይ ተከሳሾቹ ‹‹ለአመጽ ማነሳሳትና መምራት›› የሚያስችል ስልጠና ወስደዋል በሚል በተጠቀሰው ላይ ስልጠናው መቼ፣ በማን እና በምን ጉዳዮች ላይ ተሰጠ የሚለው ግልጽ ስላልሆነ አቃቢ ህግ ክሱን እንዲያሻሽል ተጠይቋል፡፡
በተጨማሪም ተከሳሾቹ አመጽ ለመምራት የስራ ክፍፍል አድርገዋል በሚል የተጠቀሰባቸው የክሱ ይዘት ‹‹ምን አይነት የስራ ክፍፍል፣ ማን ምን እንዲሰራ ክፍፍሉ ተደረገ›› የሚለውን ስለማያመለክት ይህንንም መሻሻል እንዳለበት ፍርድ ቤቱ ወስኗል፡፡
በተጨማሪም በክሱ ዝርዝር ላይ ‹‹ቡድን›› እና ‹‹ድርጅት›› በሚል (ግንቦት 7፣ ኦነግ ወይስ ሌላ የሚለውን ስለማይገልጽ) በደፈናው የቀረቡት ነጥቦች ላይ በዝርዝር መቀመጥ ስላለባቸው አቃቢ ህግ ማሻሻያ እንዲያደርግ ታዝዟል፡፡
በሌላ በኩል የተከሳሽ ጠበቆች ‹‹በኢሳት ሬድዮና ቴሌቪዥን መረጃ በመስጠት›› በሚል ተከሳሾች ላይ የቀረበው የክስ ይዘት ሆን ተብሎ ወደ ሌላ አካል (ግንቦት 7) ጋር ለማገናኘት ነው በሚል ያቀረቡትን መቃወሚያ፣ ‹‹በኢሳትና በግንቦት 7 መካከል ያለው ግንኙነት ወደፊት በማስረጃ የሚታይ ነው በሚል ፍርድ ቤቱ መቃወሚያውን ውድቅ አድርጎታል፡፡
ከተከሳሽ ጠበቆች መካከል የሆኑት አቶ አምሃ መኮንን ከችሎቱ በኋላ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፣ ፍርድ ቤቱ በተከሳሽ ጠበቆች ላይ የቀረበውን የክስ መቃወሚያ ጊዜ ወስዶ መርምሮ ውሳኔ እንዳሳለፈ ጠቅሰዋል፡፡ ይሻሻላሉ የተባሉት የክሱ ይዘቶች ላይ ጥያቄ የተነሳላቸው አቶ አምሃ የውሳኔው ዝርዝር በጽሑፍ ገና እንዳልደረሳቸው ጠቅሰው፣ ‹‹አቃቢ ህግ በታዘዘው መሰረት ክሱን የማያሻሽል ከሆነ ይሻሻላሉ የተባሉት የክሱ ይዘቶች ውድቅ የሚሆኑበት አሰራር አለ›› ብለዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ክሱ ተሻሽሎ መቅረብ አለመቅረቡን ለማየት ለህዳር 24/2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment