Search This Blog

Tuesday, February 25, 2014

የስዊስ አቃቢ ህግ የረዳት ሃይለመድህን አበራን ሰብአዊ መብቶች ያከብራል ሲሉ ቃል አቀባዩዋ ተናገሩ

-የሰዊስ አቃቢ ህግ ቃል አቀባይ ሚስ ያኔት ባልመር በረዳት ፓይለት ሃይለመድህን አበራ ዙሪያ ከኢሳት ለቀረበላቸው ጥያቄ የምርመራ ሂደቱ ያልተጠናቀቀ በመሆኑ ዝርዝር መረጃዎችን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸው ገልጸው፣ የሰብአዊ መብቱን በመጠበቅ በኩል ለተነሳው ጥያቄ ግን ስዊዘርላንድ የሰብአዊ መብቶችን በጠበቅ በኩል ታዋቂ አገር መሆኑዋን በመግለጽ የሃይለመድህንን የሰብአዊ መብቶች እንደሚያከብሩ ገልጸዋል።
ሃይለመድህን ጠበቃ ተቀጥሮለት ጉዳዩን በመከታተል ላይ ነው። የሃይለመድህንን የፍርድ ቤት ጉዳይ መከታተል ይቻል እንደሆን የተጠየቁት ቃል ሚስ በርነር፣ በአሁኑ ሰአት ስለፍርድ ቤት ሂደት ለማውራት ባይቻልም በስዊዘርላንድ አብዛኛውን ጊዜ ፍርድ ቤቶች በግልጽ ችሎት ጉዳዮችን እንደሚያዩ ተናግረዋል።
የሚቀጥለው የፍርድ ቤት ቀጠሮ ቀን ይታወቅ እንደሆን ሲጠየቁም ” እዛ ደረጃ ላይ ገና አልተደረሰም” በማለት መልሰዋል። የምርምራው ሂደት መቼ እንደሚጠናቀቅ ሲጠየቁም፣ የስዊስ የፍትህ አሰራር መረጃዎችን በሚስጢር መያዝን ስለሚያዝ፣ ምንም አይነት መግለጫ መስጠት እንደማይቻል አክለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ስዊዘርላንድ ለረዳት ፓይለት ሃይለመድህን አበራ ጥገኝነት እንደትሰጥ የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ የፊታችን አርብ ፌብሩዋሪ 28 በበርን እንደሚካሄድ በስዊዘርላንድ የ ዲሞክራሲ ለውጥ በኢትዮጵያ የስውዘርላንድ የድጋፍ ኮሚቴ ገልጿል።

No comments:

Post a Comment